‹‹ሐድይ ነፈራ›› በሐዲያ ብሔር የተለያዩ ባህላዊ ሥርዓተ ክዋኔዎች የሚከወኑበት ቦታ ነው፡፡
ይህንን ሥፍራ የብሔሩን ማኅበረ ባህላዊ እሴቶች አኗኗርን መሠረት በዞኑ ሆሳዕና ከተማ በተለምዶ ጎፈር ሜዳ ተብሎ በሚጠራው የውኃ ግድብ አካባቢ በሚገኘውና ለዚሁ ተብሎ ተለይቶ የተከለለ ሥፍራ ሲሆን፣ መጠሪያ ስያሜውም ‹‹ሐድይ ነፈራ›› ይባላል፡፡
‹‹ሐድይ ነፈራ›› በሐዲያ ብሔር ባህል የዘመን መለወጫ የ‹‹ያሆዴ›› ክብረ በዓልን የበዓሉ ተሳታፊዎች ተሰባስበው በተለያዩ ሥርዓተ ክዋኔዎች በአንድነት የሚያከብሩበት ነው፡፡
በዞኑ በዓመቱ በሚከናወኑ የልማት ፕሮጀክቶች ውስጥ ሐድይ ነፈራን አንዱ አካል አድርጎ እያለማ እንደሚገኝ የዞኑ አስተዳደር ገልጾ፣ በዚህም ሥፍራውን በመከለል የብሔሩን ባህላዊ እሴቶች የአኗኗር ሥርዓት ያካተቱ የተለያዩ ግንባታዎች በምዕራፍ ተከፋፍለው እየተገነቡ እንደሚገኙ አክሏል፡፡

ከ25 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ የሚጠይቀው ፕሮጀክቱ፣ በ50 ሺሕ ካሬ ሜትር መሬት ላይ ያረፈ ሲሆን፣ ሥራው በመጠናቀቅ ላይ መሆኑንና ግንባታውም የብሔሩን ‹‹ያሆዴ›› በዓልና ሌሎች የተለያዩ ባህላዊ ሥርዓቶችን መከወን በሚያስችል መልኩ መከናወኑን አስታውቋል፡፡
የ‹‹ያሆዴ›› ክብረ በዓል ሲከበር የበዓሉ ተሳታፊዎች መቀመጫ ቦታ፣ ለተለያዩ ሥርዓቶች መከወኛ መድረኮች፣ የባህል ሽማግሌዎች ባህላዊ ምርቃትና የዕርቅ ሥነ ሥርዓት የሚፈጽሙበት ሥፍራ በግንባታው ውስጥ ከተካተቱት ይገኝበታል፡፡
የተለያዩ ባህላዊ ጭፈራና ጨዋታዎች የሚከናወኑበት ሥፍራ፣ የፈረስ መጋለቢያ፣ ሳቴ (ችቦ) የሚቀጣጠልበትና የተለያዩ የብሔሩን ባህላዊ ጉዳዮች ለማከናወን የሚያስችሉና የቱሪስት መስህብ በመሆን መዝናኛ ሥፍራዎች ያካተተ ነው ተብሏል፡፡
ግንባታው በቅርቡ ተጠናቆ ለመጪው የሐዲያ ብሔር ዘመን መለወጫ ‹‹ያሆዴ›› ክበረ በዓል ይደርሳል ተብሎ ይጠበቃል፡፡