በዚህ ሳምንት አጋማሽ ላይ ከጓደኛዬ ጋር አዘውትረን ቡና ከምንጠጣበት ‹‹ቡና ጠጡ!›› ቤት ጎራ አልን፡፡ የጀበና ቡና ከምታፈላዋ ወጣት ጋር ተግባብተናልና እንደቀረቤታችን ሰላምታ ተለዋወጥን፡፡
ነገር ግን ከዚያች ደንበኛችን የለመድነውን ዓይነት ምላሽ አላገኘንም፡፡ ሰላምታዋ ቀዝቀዝ ብሏል፡፡ ግር ቢለንም በአንድ ጉዳይ የተረበሸች መሆኑን ግን ተገንዝበናል፡፡ ይህንኑ እያሰላሰልን ቡናችንን አዘን ተቀመጥን፡፡ ይቺ ወጣት ከአንድ ባርና ሬስቶራንት በረንዳ ላይ የጀበና ቡና በማፍላት የምትተዳደር ናት፡፡ ካወቅናት ከዓመት በላይ ሆኖናል፡፡ መስተንግዶዋ መልካም በመሆኑ፣ እንዲሁም ጥሩ ቡና ታፈላለችና ጥቂት የማይባሉ ደንበኞች አፍርታለች፡፡
የምትሠራበትን በረንዳ ከባርና ሬስቶራንቱ ተከራይታ በወር 3,000 ብር የምትከፍልበት መሆኑን ከዚህ ቀደም በጨዋታ ጨዋታ ነግራን ነበር፡፡ ልጅ ብቻዋን የምታሳድግ መሆኗን ጭምር ስለሰማን ደንበኝነታችን እሷንም ከማገዝ ጋር አስተሳስረነዋልና ቡና ለመጠጣት ስንፈልግ በጋራም ሆነ በተናጠል ከእሷ ዘንድ እንሄዳለን፡፡
ስለሕይወቷ በተወሰነ ደረጃ ማወቃችንም ትበረታ ዘንድ የምንችለውን እናደርግላታለንና ተቀራርበናል ማለት ይቻላል፡፡ ስለዚህ እኔም ሆንኩ ጓደኞቼ በመጣን ቁጥር በጥሩ መስተንግዶ ትቀበለን ስለነበር፡፡ ያንን የምናውቀውን ሰላምታዋን ስናጣ ግር ቢለን ትክክል ነበር፡፡ አንዱ ጓደኛዬ፣ ‹‹እንግዲህ በሆነ ነገር ተረብሻ ይሆናል፤›› የሚል ግምቱን ሰነዘረ፡፡ ሁላችንም ግን ይህቺ ልጅ ያለ ምክንያት እንደዚያ እንደማትሆን ተረድተናልና ቀስ ብለን ችግሯን ለማወቅ ልንጠይቃት ይገባል የሚል ሐሳብ መጥቶ ከመሄዳችን በፊት ጠጋ ብለን ጠየቅናት፡፡
ጥያቄያችን ያልጠበቀችው ሆኖባት ነው መሰል ደነገጠች፡፡ ‹‹ረበሽኳችሁ አይደል? ይቅርታ፤›› አለችን፡፡ ችግር ካለ ንገሪን ልናግዝሽ የምንችለው ነገር ካለ አለ ጓደኛዬ፡፡ ከተወሰነ ንግግር በኋላ ልጅቷ፣ ‹‹…አይ እናንተ የምትፈቱት አይደለም፡፡ ግን… አመሠግናለሁ፤›› አለችን፡፡ ከዚህ በላይ ማስጨነቅ የለብንም ብለን ማገዝ የምንችለው ነገር ካለ ግን እናግዝሻለን አልኩና ሒሳባችንን ከፍለን ወጣን፡፡
ይህ ከሆነ ከአንድ ቀን በኋላ ለብቻዬ ሄድኩኝ፡፡ ይህቺ ሴት እንደ በቀደሙ ባይሆንም አሁንም ፊቷ በአንድ ጉዳይ እየተብሰለሰለች መሆኑን ያሳብቃል፡፡ በተቻላት መጠን በቀድሞ መስተንግዶዋና ትኅትናዋ ሰላምታ ሰጥታኝ ቡና አቀረበችልኝ፡፡ በሄድኩበት ሰዓት ብዙ ቡና የሚጠጣ ባለመኖሩ አጋጣሚውን ተጠቅሜ ‹‹…የገጠመሽ ችግር አለ?፤›› አልኳት፡፡ እንደምንም ላግባባት ሞክሬ መጨረሻ ላይ የሰሞኑ ጭንቀቷ ሁለት ነገር መሆኑን መረዳት ቻልኩ፡፡ አንዱ የሬስቶራንቱ ባለቤቶች ለምትጠቀምበት ቦታ ኪራይ ጨምሪ መባሏ ነው፡፡ ሁለተኛው ደግሞ ከሰሞኑ ምርር ያደረጋት ጉዳይ ለሥራዋ የሚሆን ስኳር ለማግኘት እየገጠማት ያለው ፈተና ሥራዬን ያሳጣኛል ብላ መሥጋቷ ነው፡፡
ወትሮ ተወደደ ተብሎ አንዱ ኪሎ 60 እና 70 ብር የምትገዛው ስኳር ሰሞኑን 100 ብር መግባቱን ነገረችኝ፡፡ ሥራዬን አላቋርጥም ብዬ ለሦስት ተከታታይ ቀናት አንድ ኪሎ ስኳር 100 ብር እየገዛች ሠርታለች፡፡ በመጨረሻዎቹ ሁለት ቀናት ደግሞ እየሠራች ያለችው አንዱን ኪሎ ስኳር 120 ብር በመግዛት ነው፡፡ ስለዚህ ስኳር በዚህ ዋጋ እየገዛሁ፣ በዚህ በኩል ደግሞ ኪራይ ጨምሪ ስባል ጨንቆኝ ነው ለዚህ ነው እናንተ አትፈቱትም ያልኳችሁ አለችኝ፡፡ አዘንኩ፡፡ በድጋሚ ማድረግ የምንችለው ነገር ካለ እናግዝሻል፣ ግን አትጨነቂ ብዬ ላረጋጋት ሞክሬ ወጣሁ፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ የስኳር አቅርቦት ችግር አሁንም የዜጎች ሰቀቀን ሆኖ መቀጠሉ የበለጠ አሳዘነኝ፡፡ እንደ ይህች ወጣት በየአካባቢው ያሉ የጀበና ቡና ሠራተኞች በሙሉ ታዩኝ፡፡ ጠዋት ጠዋት ልጆቻቸውን ሻይና ዳቦ በማቅረብ ቁርስ የሚሰጡ እናቶች ከእጥፍ በላይ ዋጋው የተሰቀለውን የስኳር ዋጋ እንዴት ይቋቋሙት ይሆን ብዬ ሁሉ አሰብኩ፡፡ ችግሩ የብዙዎች ሸማች መሆኑንም መገመት አያዳግትም፡፡ ገጠመኜ በኋላ ስለሰሞናዊው የስኳር ዋጋ መተኮስ ምክንያት ለማወቅ ሞከርኩ፡፡ ካለፉት 15 ቀናት ወዲህ ለሸማቾች ስኳር በማቅረብ የሚታወቁ የሸማች ማኅበራት ዘንድ ስኳር የለም፡፡ ብዙዎቹ መደብሮች ውስጥ ግን ተወደደ የተባለው ስኳር የሚከፍል እስካለ ድረስ በሽ ነው፡፡ ብር ያለው ይገዛል፡፡ ደንበኞቿን ማጣት ያልፈለገችው እንደ የቡና ደንበኛችን ያሉ የጀበና ቡና አፍልተው የሚሰጡ እንስቶች እየከሰሩም ቢሆን ቡናቸውን እየሸጡ ነው፡፡ ከወጣቷ መረዳት እንደቻልኩት በዚህ በመጣው የስኳርና የስኳር ዋጋ በአሥር ብር ቡና መሸጥ አያዋጣም፡፡ እየከሰርኩ ሸጬ ልጄን በምን ላሳድግ ነው የሚል ነው፡፡ ዋጋ ብጨምር ደግሞ ተጠቃሚ ላይኖር ይችላል የሚል ሥጋቷን ሁሉ ዕንባዋ እያቀረረ ነበር የነገረችኝ፡፡ በነገራችን ላይ የእኛ ደንበኛ ዋጋ አትጨምር እንጂ በዚሁ ስኳርና ቡና መወደድ ሳቢያ 10 ብር ይሸጡ የነበሩትን ቡና 15 ብር አድርገዋል፡፡
ለማንኛውም ይህ የስኳር ችግር የብዙዎች ሸማቾችና ኑሮን ለማሸነፍ የሚጣጣሩ ወጣቶች ሰሞናዊ ጭንቀት ነው፡፡ የአገራችን የስኳር ገበያ እንዲህ እየተወነባበደ የአንድ ጎልማሳ ዕድሜ ላይ መድረሱ እጅግ ያሳዝናል፡፡ የግብይት ሥርዓቱ ያለበትን ብልሽት ደጋግመን መግለጻችንና የመፍትሔ ያለህ ብለን ብንጮህም የሚሰማ የለም፡፡ አሁንም በሸማች ማኅበራት ጠፋ የተባለ ስኳር በየመደብሩ የመገኘቱ ነገር የሚነግረን ነገር አለ፡፡ ስኳር በየመደብሩ መኖሩ መልካም ቢሆንም፣ አንድ ኪሎ እስከ 120 ብር የሚሸጥበት ምክንያት እጅግ ግራ ያጋባል ብቻ ሳይሆን ግብይቱ ውስጥ ያለውን ብልሽት ሁሉ ያሳየናል፡፡
በቂ ስኳር አለ እየተባለ አንድ ኪሎ 120 ብር ሲሸጥ መንግሥት ምን እየጠበቀ ነው እንድንል ያደርገናል፡፡ የአገራችን ነጋዴዎችም 50 ብር ባልሞላ ዋጋ የተረከቡትን ስኳር 120 ብር ድረስ ሲሸጡስ ምን ይሰጣቸው ይሆን? ነገሩን እንደ ቀላል ማየት የለብንም፡፡ ከሁለት ሦስት ወራት በፊት የስኳር ገበያ እየተበላሸ ነው፡፡ ለኅብረተሰቡ ይቀርባል የተባለው ስኳር በጎን በአትራፊዎች እየተጠለፈ ነውና አንድ ነገር ይደረግ ስንል ሰሚ በመጥፋቱ ይኼው የተፈራው ደርሶ አንድ ኪሎ ስኳር 120 ብር እየተቸበቸበ ነው፡፡ በዚህ ወቅት ለብዙዎች ሸማቾች መሠረታዊ የሚባለውን የስኳር አቅርቦትና አጠቃላይ ግብይት ለምን ማስተካከል እንዳልተቻለ ዛሬም ግራ ያጋባል፡፡ ለችግሩ መፍትሔ ባለመስጠቱ ወቅት እየጠበቀ ሸማቾች ያልተገባ ወጪ የሚያወጣበት ምክንያት እንቆቅልሽ ነው፡፡ በቂ ስኳር እየቀረበ ነው ከተባለ እጥረቱ የሚፈጠርበት ምክንያት ያለው የስኳር ገበያ ሥር የሰደደ ሌብነት በሁሉም ሥፍራ በመኖሩ፣ መሆኑን አሁንም ደግመን መግለጽ እንወዳለን፡፡ ሸማቾች ማኅበራት ዘንድ ጠፍቶ በየሱቁ የመገኘቱ ሚስጥርም ይህ ነው፡፡ ሸማቾች ማኅበራት በደላሎችና በባለመደብሮች መካከል ለዓመታት የዘለቀው የሌብነት ትስስር እስካልተበጠሰ ድረስ ሸማቾች ፍዳቸው ይቀጥላል፡፡ በዚሁ ሰበብ እንደ የቡና ደንበኛችን ያሉ ኑሮን ለማሸነፍ የሚታትሩ ዜጎች ደግሞ ሠርቶ የመኖር መብታቸውን እየነካ ነው፡፡ የዋጋ ንረቱንም እያባሰው ነው፡፡ በነገራችን ላይ ባልተገባ ምክንያት በሚፈጠር የምርት እጥረት ትኩረት ተደርጎበት ቁጥጥር ይደረግበት ብለን ደጋግመን የምንወተውተው ችግሩ የአንድ ወቅት ብቻ ያለመሆኑ ነው፡፡ በተለይ መሠረታዊ የሚባሉ እንደ ስኳር ያሉ ምርቶች እጅግ በተጋነነ ዋጋ መሸጣቸው ስኳርን ግብዓት አድርገው የሚዘጋጁ የተለያዩ ምርቶች ዋጋ እንዲጨምሩና የዋጋ ንረቱን ስለሚያብሱ ጭምር ነው፡፡ ስኳርን እንደ ምሳሌ ጠቀስን እንጂ በብዙ ምርቶች ላይ የሚደረግ ያልተገባ የዋጋ ጭማሪ በተያያዥ የዋጋ ንረት ምክንያት እየሆነ ነው፡፡ በተደጋጋሚ እንደሰማነው እንደ ብረትና ሲሚንቶ ያሉ ምርቶች ግብይት አሳፋሪ በሚባል ደረጃ መበላሸትና የሚሸጡበት ዋጋ ንረት ከአቅም በላይ በመሆኑ የኮንስትራክሽን ኢንዱስትሪው እንጀራ ሆኗቸው የነበሩ ብዙዎች ከሥራ እየተቀነሱ ስለመሆኑ የሚነግረን ነገር ቁጥጥር የሌለበት የግብይት ሥርዓትና ያልተገባ የዋጋ ጭማሪ የሥራ ዋስትናን እየተፈታተነና ብዙዎቻችንን ሥራ እያሳጣ ነው፡፡ በመሆኑም የስኳር ገበያን እንኳን መቆጣጠር ያልቻለ፣ በሕግ ኃላፊነት የተሰጠው መንግሥታዊ ተቋማት የሌብነቱ አካል ሆኗል፣ ወይም ቅልጥ ያለ እንቅልፍ ውስጥ ናቸው ማለት ነው፡፡ አሁንም ግን ‹‹እባካችሁን ከብዝበዛ አድኑን፣ ሥራ አጥም አታድርጉን›› የሚለው የሸማቾች ድምፅ ይደርሳችሁ ዘንድ ዛሬም ሸማቾችና ተገልጋዮች ይማጸናሉ፡፡