- ፌዴሬሽኑ ጉዳዩ ‹‹በወሬ ደረጃ›› ያለ መሆኑን ገልጿል
- ሆቴሉን ከታላቁ ኢዮ ቤልዩ ቤተ መንግሥት ፕሮጀክት ጋር ለመቀላቀል መታሰቡ ተጠቁሟል
የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን በባለቤትነት እያስተዳደረው የሚገኘውንና እስጢፋኖስ ቤተ ክርሲቲያ ፊት ለፊት የሚገኘው ሕንጻ፣ መንግሥት በልዋጭ መልክ ሊወስደው መሆኑ ተሰማ፡፡ የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን በበኩሉ ‹‹በወሬ ደረጃ›› እንጂ ስለጉዳዩ እስካሁን ምንም ዓይነት ውሳኔ ላይ አልተደረሰም ብሏል፡፡
ሕንጻው ከ12 ዓመታት በፊት የብሔራዊ ፌዴሬሽኑ ፕሬዚዳንት በነበሩት የወ/ሮ ብስራት ጋሻውጠና ካቢኔ አማካይነት፣ ፌዴሬሽኑ በባለቤትነት እንዲያስተዳድረው፣ ፌዴሬሽኑን ለማገዝ በሚል በሽያጭ መልክ ተላልፎ የተሰጠው መሆኑ ይታወሳል፡፡
ፌዴሬሽኑ ከዚህ ሕንጻ በተጨማሪ በአሁኑ ወቅት በዋና ጽሕፈት ቤትነት እየተገለገለበት ያለውንና ጉርድ ሾላ አካባቢ የሚገኘውን ሕንጻ በወቅቱ በነበሩት የወ/ሮ ብስራት ጋሻውጠና አመራሮች አማካይነት የተገነባ መሆኑ አይዘነጋም፡፡
ይህንኑ ተከትሎ ከተቋም ባለቤትነት አልፎ፣ በውጤት ደረጃ በአኅጉር አቀፍና በዓለም አቀፍ ደረጃ በቀዳሚነት የሚጠቀሰው የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሸን፣ በራሱ በጀት የሚተዳደር ብሔራዊ ተቋምም ከሆነ ውሎ አድሯል፡፡
ሕንጻው ቀደም ሲል ይታወቅበት የነበረውን የሆቴል አገልግሎት እንዲያቆም ከተደረገ በኋላ፣ ቀድሞ የወጣቶችና ስፖርት ሚኒስቴር እንዲሁም የፌዴራል ስፖርት ኮሚሽን ዋና መሥሪያ ቤት፣ በአሁኑ ወቅት ደግሞ ባህልና ስፖርት ሚኒስቴር በከፊት ጽሕፈት ቤት አድርጎት በኪራይ እየተገለገሉበት የሚገኝ መሆኑ ይታወቃል፡፡ በዚሁ መሠረት ብሔራዊ ፌዴሬሽኑ ከሕንጻው ኪራይ በዓመት እስከ 11 ሚሊዮን ብር የሚጠጋ ገቢ ሲያገኝ ስለመቆየቱ ጭምር የሚናገሩ አስተያየት ሰጪዎች አሉ፡፡
ስማቸው እንዲጠቀስ ያልፈለጉ ምንጮች ለሪፖርተር እንደገለጹት ከሆነ፣ ባህልና ስፖርት ሚኒስቴር ዋና ጽሕፈት ቤቱን ብሔራዊ ባንክ ጀርባ ወመዘክር ቤተ መጻሕፍት አጠገብ ወደሚገኘው ባህልና ስፖርት ሕንጻ ጠቅልሎ ሊያዘዋውር እንደሆነ ነው፡፡
ምንጮቹ የፌዴሬሽኑን ሕንጻ ጉዳይ አስመልክቶ፣ ቀድሞ ብሔራዊ ሆቴል ተብሎ የሚታወቀውንና እስጢፋኖስ ቤተ ክርሲቲያን ፊት ለፊት የሚገኘውን ሕንጻ ምትክ ሰጥቶ ለመውሰድ፣ ለፌዴሬሽኑ ጥያቄ ማቅረቡን ነው የሚያስረዱት፡፡
ከጥያቄው በተጨማሪ በጉዳዩ ከሚመለከታቸው ፌዴሬሽኑ አመራሮች ጋር የመከረ ስለመሆኑ ጭምር የሚናገሩት እነዚሁ ምንጮች፣ ይሁንና ሕንጻውን በምትክ ለመውሰድ የፈለገው ለምን ምክንያት እንደሆነ ግን ከመግለጽ ተቆጥበዋል፡፡ በሌላ በኩል ለዚህ ውሳኔ የበቃው፣ በፌዴሬሽኑ ሕንጻ አጠገብ የሚገኘው ጊዮን ሆቴልና ታላቁ እዩ በልዩ ቤተ መንግሥትን ጨምሮ ለሌላ ፕሮጀክት ለማዋል ካሰበው ዕቅድ ጋር ሊያያዝ እንደሚችል የሚጠቅሱ አልጠፉም፡፡
የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ጊዜያዊ ዋና ጸሐፊ የሆኑት አቶ ዮሐንስ እንግዳ በበኩላቸው፣ ጉዳዩ ‹‹በወሬ ደረጃ›› ካልሆነ እስካሁን ባለው ምንም ዓይነት ድርድርም ሆነ ውይይት እንዳልተደረገ ተናግረዋል፡፡ ይሁንና ለጉዳዩ ቅርበት ያላቸው ምንጮች፣ የፌዴሬሽኑ አመራሮች በጉዳዩ ተነጋግረው ውሳኔን ለመቀበል ፍላጎት ማሳየታቸውን ነው የሚናገሩት፡፡