- ክቡር ሚኒስትር፣ እንዲያው ይቅርታ ያድርጉልኝና አንድ ጥያቄ ልጠይቅዎት እችላለሁ?
- ምን ዓይነት ጥያቄ ቢሆን ነው? ለማንኛውም ጠይቀኝ ችግር የለውም።
- በእርስዎ እምነት ገዥው ፓርቲ ከሠራቸው ስኬታማ ሥራዎች ግንባር ቀደም የሚሉት ምንድነው?
- ከባድ ጥያቄ ነው፡፡
- እንዴት?
- ምክንያቱም ለማበላለጥ ይከብዳል፣ ከወለድካቸው ልጆችህ ወይም ከእጅህ ጣቶች መካከል የቱን አስበልጠህ ትወዳለህ እንደ ማለት ነው፣ ለእኔ ሁሉም ስኬቶች እኩል ናቸው ማለት ይቀለኛል።
- አርቲስት ነው የመሰሉኝ ክቡር ሚኒስትር።
- እንዴት?
- እነሱ ናቸው ብዙ ጊዜ እንዲህ ዓይነት መልስ የሚሰጡት፣ በተለይ በሚዲያ በሚተላለፉ የበዓል ፕሮግራሞች ላይ።
- ለመሆኑ ለምንድነው የጠየቅከኝ? ልትነግረኝ የፈለግከው ነገር አለ?
- እንደዚያ ሳይሆን ነገሩ ቢያስገርመኝ ነው እርስዎን መጠየቅ የፈለግኩት።
- ያስገረመህ ነገር ምንድነው?
- ገዥው ፓርቲ ከሠራቸው ሁሉ የሚበልጠው ትልቁ ነገር የአስተዳደር ወሰኑን ማካለሉ ነው መባሉ።
- ለምን አስገረመህ?
- ትልቅ ነገር አይደለማ፡፡
- እንዴት? ለምን?
- ጥያቄውን ያነሳነው እኛው ነን፣ ለፖለቲካ ትግል ብለን ራሳችን ያነሳነውን ጥያቄ ሥልጣን ላይ ወጥተን መልስ መስጠታችን ተዓምር አይደለም ብዬ ነው።
- ጅል፡፡
- ክቡር ሚኒስትር እየሰደቡኝ ነው?
- ስድብ አይደለም።
- ጅል አሉኝ እኮ?
- ስድብ አይደለም ስልህ፡፡
- ታዲያ ምን ማለት ነው?
- እንደ ፓርቲ አባል ሳይሆን አንደ ማኅበረሰብ አንቂ ወይም አክቲቪስት ነው የጠየቅከው ለማለት ነው፣ እነሱ ናቸው የነቁ መስሏቸው እንዲህ ዓይነት ጥያቄ የሚያነሱት።
- በእርግጥ ይህኑኑ ጥያቄ አንዳንድ ታዋቂ ሰዎች በማኅበራዊ ትስስር ገጾች ሲያነሱ ተመልክቻለሁ ቢሆንም ተገቢ ጥያቄ ይመስለኛል።
- ጅላ ጅል፡፡
- ጅላ ጅል አሉኝ ክቡር ሚኒስትር? ጆሮዬ መሆን አለበት፡፡
- ጆሮህ አይደለም፡፡
- እና ምን አጠፍቼ ነው የሰደቡኝ ታዲያ?
- ስድብ አይደለም፡፡
- ጅላ ጅል ስድብ ካልሆነ ምን ሊሆን ነው ክቡር ሚኒስትር?
- ለራሳቸው ሳይነቁ ማኅበረሰብ አንቂ ነን የሚሉ ጅል ናቸው አላልኩህም?
- ባልስማማበትም ብለውኛል።
- አዲሱ ዕይታችን ነው፣ የአንተ መስማማት አስፈላጊ አይደለም።
- እሺ… ምን ይደረጋል… ይሁን፣ ስለዚህ ጅላ ጅል ማለት ምን ማለት ነው?
- ጅሎችንና ሐሳባቸውን ለሚከተሉ የተሰጠ ስያሜ ነው።
- በአዲሱ የድርጅታችን ዕይታ ማለት ነው?
- አዎ፣ ልክ ነው፡፡
- እኔ የምልዎት ክቡር ሚኒስትር?
- እህ…
- ሐሳቦችን ለመፈረጅ ጊዜ ከምናጠፋ ጥያቄዎችን ብንመልስ አይሻልም?
- አሁን ደግሞ ምን እንደምትባል ታውቃለህ?
- ምን እባላለሁ?
- ጅላንፎ!
[ክቡር ሚኒስትሩ ከአንድ አብሮ አደግ ወዳጃቸው ጋር በመኖሪያ ቤታቸው ሆነው ስለአገር ጉዳይ እየተጨዋወቱ የዕረፍት ቀናቸውን እያሳለፉ ነው]
- እኔ ምልህ ክቡር ሚኒስትር?
- እንዲያው ይኼን ክቡር ሚኒስትር ማለት ተወኝ አላልኩህም?
- አንተ ባትፈልግም ለተቋሙ ክብር መንፈግ ባህላችን አይደለም፣ ይልቅ ልጠይቅህ የነበረውን አስረሳኸኝ፡፡
- ምን ልትጠይቅ ነበር?
- አዎ፣ አስታወስኩት፣ እኔ የምልህ?
- እህ…
- መንግሥት በተደጋጋሚ ጊዜ ለሰላም ዝግጁ ነኝ እያለ በይፋ እየገለጸ ነው። አይደለም?
- ትክክል ነው እሱማ፣ እነሱም ሰላም እንፈልጋለን ይላሉ፡፡ ታዲያ ሰላም ማውረድ ለምን አልተቻለም? ችግሩ ምንድነው?
- ግራ ተጋብተው ግራ እያጋቡን መሆኑ ነው ችግሩ።
- እንዴት?
- ሰላም እንፈልጋለን ይላሉ፣ ግን ደግሞ ግራ የሚያጋባ ቅደመ ሁኔታ ያስቀምጣሉ።
- ምንድነው ግራ የሚያጋባው ቅድመ ሁኔታ?
- ለሰላም ዝግጁ ከሆናችሁ በቅድሚያ መግባት አለባችሁ ይሉናል፡፡
- መግባት አለባችሁ ይሉናል ነው ያልከው ክቡር ሚኒስትር?
- አዎ።
- ወዴት?
- እነሱ ወደ የሚያስተዳድሩት ክልል።
- ለምን? ምን እንድታደርጉ ነው?
- ቴሌ፣ ባንክና ሌሎች አገልግሎቶችን እንድንጀምር።
- አገልግሎት ለማግኘት ብለው ነዋ፡፡
- አዎ፣ ግን ደግሞ ንግድ ባንክም ሆነ ቴሌ የፌዴራል መንግሥት ተቋማት ናቸው።
- እሱማ ልክ ነው፣ በተጨማሪም የፌዴራል መንግሥት በየትኛውም አካባቢ የመሰማራት መብት አለው።
- አሱን ተወውና ያነሱትን ጥያቄ ተቀብለን ለመግባት ስንዘጋጅ ደግሞ ውጡ ይሉናል።
- ከየት? ገና ሳትገቡ?
- ከምዕራቡ ወሰን ውጡ ይሉናል።
- ሠራዊቱን ማለታቸው ነዋ፡፡
- አንተ ራስህ የፌዴራል መንግሥት በየትኛውም አካባቢ መሰማራት ይችላል ስትል አልነበር እንዴ?
- በእርግጥ ብያለሁ።
- ታዲያ የፌዴራል መንግሥቱን ሠራዊት ለምን ይውጣ ይላሉ?
- ተመልከት አንዴ ሠራዊቱ ይውጣ ይሉናል፣ እዚያው ደግሞ አገልግሎት ሰጪ የፌዴራል ተቋማት ካልገቡ ይሉናል።
- በመግለጫችሁ ላይ በኋላ ያላችሁት ነገር አሁን ነው የገባኝ፡፡
- በኋላ ያልነው ምንድነው?
- መግባትና መውጣት!