Saturday, March 25, 2023
- ማስታወቂያ -
- ማስታወቂያ -

የኢታኖል ቤንዚን ድብልቅ አቅርቦትን ማስቀጠል ከየወሩ የነዳጅ ግዥ ግማሽ ሚሊዮን ዶላር ማዳን ያስችላል ተባለ

- ማስታወቂያ -

ተዛማጅ ፅሁፎች

ኢትዮጵያ ከፍተኛ የውጭ ምንዛሪ ከምታወጣባቸው የገቢ ምርቶች ውስጥ ነዳጅ በዋናነት የሚጠቀስ ነው፡፡ ይህንን ከፍተኛ የሆነ ወጪ በተወሰነ ደረጃም ቢሆን ለመቀነስ ይረዳል በሚል ከቤንዚን ጋር በማደባለቅ ለአገልግሎት የሚውል ሥራ አንዱ ነበር፡፡ ዓለም አቀፍ ልምዶችን በመቀመርና ኢትዮጵያ ኢታኖል የማምረት አቅሟን ከግምት በማስገባት ‹‹E5›› ወይም አምስት በመቶ ኢታኖልን 95 በመቶ ቤንዚን በማደባለቅ ለገበያ እንዲቀርብ በተወሰነው መሠረት ለተወሰኑ ዓመታት ሲሠራበት ቆይቷል፡፡ 

ይህንን የሚመራና የሚቆጣጠር ራሱን የቻለ ተቋምም ተቋቁሞ እንደነበር ይታወሳል፡፡ የኢትዮጵያ ነዳጅ አቅራቢ ድርጅት ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ታደሰ ኃይለ ማርያም ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ ኢታሎኑን ከቤንዚን ጋር በመደባለቅ ለገበያ የማቅረቡ ሥራ ቢገፋ ኖሮ ብዙ ጠቀሜ ይሰጥ ነበር፡፡ እንደ አገር ከፍተኛ ጠቀሜታ ነበረው፡፡ ሆኖም ከቤንዚን ጋር የሚቀርበውን አምስት በመቶ ኢታኖል ሲያቀርቡ የነበሩ ፊንጫና መተኸራ ፋብሪካዎች በቂ ምርት ማቅረብ ባለመቻላቸው የማደባለቁ ሥራ ሊቋረጥ ችሏል ብለዋል፡፡ በወቅቱ እነዚህ ስኳር ፋብሪካዎች በቀን ያቀርቡት የነበረው ከ50 እስከ 60 ሺሕ ሌትር ኢታኖል ከቤንዚን ጋር ተደባልቆ ለአዲስ አበባና ለአካባቢው ከተሞች ይቀርብ እንደነበር አስታውሰዋል።

በዚህን ያህል መጠን በሱሉልታ ነዳጅ ዲፖ ተደባልቆ የሚቀርበው ምርት ብቻ በወቅቱ በየወሩ ለነዳጅ ግዥ ይወጣ የነበረውን ከግማሽ ሚሊዮን ዶላር ያላነሰ ወጪ ለማዳን በማስቻሉ ጥቅሙን በመረዳት የኢታኖልና ቤንዚን ድብልቅ ምጣኔን ወደ አስር በመቶ ለማሳደግ ጭምር ታቅዶ ተጨማሪ ጥናትና ዝግጅት ተደርጎ እንደነበርም አቶ ታደሰ ያስታውሳሉ፡፡  

የኢታኖልን ድብልቅ መጠኑን ወደ አሥር በመቶ ለማሳደግና በአዲስ አበባና በአካባቢው የተወሰነውን ኢታኖል ድብልቅ ቤንዚን ሥርጭት በመላ አገሪቱ ለማዳረስ ታቅዶ እንደነበረ፣ ይህንን ዕቅድ ለማሳካትም በወቅቱ ከነበሩ ስኳር ፋብሪካዎች በተጨማሪ ሌሎች አዳዲስ አሥር ስኳር ፋብሪካዎች እንደሚገቡ ታሳቢ መደረጉን ገልጸዋል፡፡ 

ነገር ግን ታሳቢ የተደረጉት አዳዲስ ፋብሪካዎች ግንባታ መዘግየት ዕቅዱን ለማሳካት እንዳላስቻለ፣ ይባስ ብሎ ኢታኖልን ያመርቱ የነበሩት ስኳር ፋብሪካዎች የምርት መጠንም በማሽቆልቆሉ ለአዲስ አበባና አካባቢዋ ይቀርብ የነበረው የኢታኖል ድብልቅ ቤንዚን ስርጭት እንዲቋረጥ ማስገደዱን ገልጸዋል፡፡ በነዳጅና በነዳጅ ውጤቶች ሙያ ላይ ለረዥም ዓመታት የሠሩት ሰርካለም ገብረ ክርስቶስ (ዶ/ር)፣ ለሪፖርተር እንደገለጹም ኢታኖል ድብልቅ ቤንዚን እንደ ኢትዮጵያ ላለ አገር ጠቃሚ ነው፡፡ ይህንን አሰራር ማስፋት ይቻል እንደነበር የገለጹት ባለሙያው ፣ በዚህ መንገድ የቤንዚን ወጪን ከ10 እስከ 15 በመቶ መቀነስ ቢቻል ከወጪ ቅናሹ ይገኝ የነበረው ጥቅም ቀላል የሚባል እንዳልሆነ አስረድተዋል። እንደ ብራዚልና ኩባ ያሉ አገሮች የኢታኖል ድብልቅ ቤንዚንን እስከ 40 በመቶ ወይም E40 ማድረሳቸው የጠቀሜታው ማሳያ መሆኑን የሚያነሱት ሰርካለም (ዶ/ር)፣ እነዚህ አገሮች ቤንዚን ላይ ብቻ ሳይሆን በናፍጣ ላይም እንደሚጠቀሙ አስረድተዋል፡፡ የእነዚህ አገራት ልምድ የሚያሳየው የቤንዚን ወጪያቸውን በከፍተኛ ደረጃ መቀነስ መቻለቸውን እንደሆነ በመጥቀስ ፣ ኢትዮጵያም ኢታኖልን ለማምረት የሚያስችል አቅምም ሆነ ዕድሉ ስላላት ይህንን አሰራር በማስቀጠል ተጠቃሚ መሆን እንዳለባት ይመክራሉ።

ከቅርብ ወራት ወዲህ ዓለም አቀፍ የነዳጅ ዋጋ ከፍ ማለት ኢታኖልን ድብልቅ ቤንዚን የሚጠቀሙ አገሮች ኢታኖል በሰፊው ወደ መጠቀም በመግባት ሸክማቸውን ለማቃለል እየሞከሩ ሲሆን፣ ከሰሞኑ አንዳንድ የአሜሪካ ግዛቶችም የኢታኖልን የድብልቅ መጠንን እስከ 15 በመቶ የማሳደግ ውሳኔ ማሳለፋቸውም በምሳሌነት የሚጠቀስ ነው።

በኢትዮጵያ ኢታኖልን ከቤንዚን በመደባለቅ ይተገበር የነበረው አሠራር ከተቋረጠ ከአራት ዓመታት በላይ በላይ እንደሆነው የጠቆሙት አቶ ታደሰ፣ ይህ አሠራር እየጎለበተ መጥቶ ቢሆን ኖሮ፣ በተለይ የነዳጅ ዋጋ በናረበት በአሁኑ ወቅት ኢታኖልን ከቤንዚን መደባለቅ የቤንዚን የችርቻሮ ዋጋን በመቀነስ ለመንግስትም ሆነ ለማሕበረሰቡ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያበረክት ነበር ብለዋል፡፡ የኢታኖልና ቤንዚን ድብልቅ ለገበያ ይቀርብ በነበረበት ወቅት ይኸው የዋጋ ቅናሽ በግልጽ ተስተውሎ ነበር፡፡ የአንድ ሌትር ቤንዚን ዋጋ 21 ብር 87 ሳንቲም ይሸጥ በነበረበት ወቅት ኢታኖል ድብልቅ 21 ብር ከ33 ሳንቲም ይሸጥ እንደነበርና በሁለቱ መካከል በአማካይ 55 ሳንቲም ልዩነት እንደነበረ ሪፖርተር የተመለከታቸው መረጃዎች ይጠቁማሉ።

ይህ ልዩነት ቀላል የማይባል መሆኑን የሚጠቅሱት አቶ ታደሰ፣ አገልግሎቱ ባይቋረጥና የሚደባለቀውን የኢታኖል መጠን እየጨመሩ መሄድ ቢቻል እንደ አገር ትልቅ ጠቀሜታ ያስገኝ ነበር ይላሉ፡፡ ሰርካለም (ዶ/ር) ም በዚህ ሐሳብ ይስማማሉ፡፡ አብዛኛው የቤንዘን ተሽከርካሪ አዲስ አበባ ላይ በመሆኑ ከ70 እና 75 በመቶ በላይ የኢትዮጵያ ቤንዚን ፍጆታ በአዲስ አበባና በዙሪያዋ እንደሚቀርብ የገለጹት ሰርካለም (ዶ/ር)፣ በዚህም ምክንያት የኢታኖል ድብልቅ ቤንዚን አዲስ አበባ ላይ እንዲተገበር መደረጉ ተገቢ እንደነበር ገልጸዋል። ነገር ግን በአምስት በመቶ የተጀመረው ሥራ ወደ 10 በመቶ ያድጋል ተብሎ ሲጠበቅ መቋረጡ ትክክል እንዳልሆነ ያስረዳሉ። ይህም በአግባቡ አቅዶ መተግበር ላይ አገራዊ ችግር ያሳያል ይላሉ፡፡ ኢታኖል ከቤንዚን ደባልቆ መጠቀም ጠቀሜታው ታውቆ ሥራው ከተጀመረ በኋላ መቋረጡም የመንግሥትን ትከሩት ማጣት ያመለክታል ብለዋል፡፡ ከዚህ በፊት ለኢታኖልን ድብልቅ ተብሎ የተቋቋመው መሥሪያ ቤት ዛሬ የት እንዳለ አይታወቅም የሚሉት ሰርካለም (ዶ/ር)፣ በተጠና መልኩ ሥራው ቀጥሎ ቢሆን ኖሮ ጠቀሜታው ለአገር ነበር ሲሉ ቁጭታቸውን አካፍለዋል።

አሁንም ይህንን አገልግሎት መልሶ መጀመር ብዙ ጠቀሜታ እንደሚኖረው የጠቀሱት አቶ ታደሰ በበኩላቸው፣ አዳዲስ የስኳር ፋብሪካዎች ኢታኖልን በብዛት የሚያመርቱ ከሆነ አሁንም ኢታኖል ድብልቅ ቤንዚንን መልሶ ለገበያ ማቅረብ የሚቻልበት ትልቅ ዕድል መኖሩን ጠቁመዋል።

ከቤንዚን ጋር የሚደባለቀውን ኢታኖል የሚያመርቱት የአገሪቱ ስኳር ፋብሪካዎች አሁንም ኢታኖል እያመረቱ ቢሆንም፣ የሚያመርቱት የኢታኖል መጠን ግን በሚፈለገው ልክ ባለመሆኑ ምርቱ በአሁኑ ወቅት ለአክኮልና እንደ “ሳኒታይዘር” ላሉ የንጽህና መጠበቂያ ምርቶች ግብዓትነት ብቻ እየዋለ ነው።

በተለይ ከኮቪድ-19 ወረርሽኝ መከሰት በኋላ በየፋብሪካዎቹ የሚመረተው ኢታኖል የንጽህና መጠበቂያ ምርቶችን ለማምረት በግብዓትነት እንዲውል በመደረጉ ለቤንዚን የሚሆን ኢታኖል ማቅረብ እንዳይታሰብ ማድረጉ ይነገራል፡፡ በሌላ በኩል ኢታኖል ረዥም ጊዜ መጠቀም ተሽከርካሪ ላይ ችግር አለው የሚል አስተያየት የሚሰነዘር ቢሆንም፣ ሰርካም (ዶ/ር) ግን ያን ያህል ችግር እንደሌለው ጠቁመዋል፡፡ ስለዚህ ጠቀሜታው የጎላ ስለሆነ አሁንም ለመሥራት ጊዜው አልረፈደም ሲሉ መክረዋል፡፡

spot_img
- Advertisement -spot_img

የ ጋዜጠኛው ሌሎች ፅሁፎች

- ማስታወቂያ -

በብዛት ከተነበቡ ፅሁፎች