Saturday, March 25, 2023
- Advertisement -
- Advertisement -

የተመረጡ ፅሑፎች

ምዝገባ ላይ ነን!

ከጀሞ ወደ ፒያሳ ለመሄድ ጉዞ ሊጀመር ቢሆንም በዚህ ክረምት ታክሲ የሚባል ነገር የለም፡፡ የምፀት፣ የኃፍረትና የቁጭት ስሜት የኮሰኮሰው ሁሉ ከንፈሩን እየመጠጠ ቆሟል፡፡ የመኖር ጉጉት የቀዘቀዘበት ሆኗል ጎዳናው፡፡ የእንቅስቃሴው ልግመኝነት ይህን ያሳብቃል፡፡ ከቶ ከብሶት ወዲያ የመኖርን ጣዕም የሚያበላሽ ምን አለ? ጎዳናው ያስፈራል፡፡ የታመቀ የብሶት ስሜት ታክሲ ጠባቂዎች ላይ ይታያል፡፡ ዕርምጃዎች ሁሉ እንዳልደላቸው ያስታውቃሉ፡፡ ድሎቱ ቀርቶባቸው ሊወገዱላቸው የሚገቡ እንቅፋቶች እንኳ ፈቀቅ ያልተደረጉላቸው እልፍ ናቸው፡፡ ይኼው ነው የዚህ ጎዳና ታሪክ፡፡ ሲመጣና ሲሄድ የኖረው ሁሉ አንድ ዓይነት እንቅፋት እያደናቀፈው የአቅሙን ያህል ሳይሮጥ ያበቃለታል፡፡ ይህ ነው የዘመናችን ታሪክ፡፡ ላይድን ቁስሉ ሲያጠግግ፣ ላይሽር ጠባሳው ሲከስም፡፡ አገሪቱንም ከፍ እንዳትል የሚኮረኩማት ችግር ከጊዜ ጊዜ እየላቀ፣ ሸለቆውና ስርጓጉጡ መንገድ በረዘመ መጠን የመጣው ከሄደው የባሰ ያደክማል፡፡ ትውልድ ሁሉ ራዕይ ርቆት የኑሮ ጣሪያው የዛሬን ብቻ ያለ ይመስላል፡፡ ምን ይደረግ ታዲያ!

ጎዳናው ላይ ያልተጻፈ ነገር የለም፡፡ ብሶት፣ እልህ፣ ታጋሽነት፣ አርቆ አሳቢነት፣ ተስፋ መቁረጥ፣ ከንቱ የመሆን ስሜት፣ ወዘተ በየዓይነቱ አለ፡፡ ስሜት ነው የሰው ልጅ ፍላጎት መገለጫ ድምፅ፡፡ ሁሉም በመሰለው ለመሮጥ አሰፍስፎ የአቅሙን ያህል እንዳይሮጥ ዙሪያውን ከትራንስፖርት ችግር እስከ አስተሳሰብና አመለካከት ችግር መንገድ ተዘጋግቶበት ቆሟል፡፡ ከሚታየው እስከ የማይታየው ሁሉም የመንገድ ጋሬጣ ነው፡፡ እንደዚህ ነው የዚህ ጎዳና ህላዌ ሚስጥር፡፡ የፈቀዱትን ለመሆን ባልፈቀዱት ሥፍራና ሰርጥ ውስጥ ወድቀው የሚነሱበት፡፡ ለዚህም ብዙ ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ ትንታኔዎች የሚቀርቡበት፡፡ ድንገት ከዚህ ሐሳባዊ ፍልስፍናና ምርምር ወጥተን ታክሲ ሲመጣ ስናይ የቆምነው መሄጃ ስላጣን ሊመስል ይችላል፡፡ ቀደም ቀደም ያልነው በመጣው ብቸኛ ታክሲ ውስጥ ገብተን ተሳፍረናል፡፡ ተጓዥ ይኑር እንጂ መሄጃማ መቼ ጠፍቶ ያውቃል!

በዋናው የሕይወት ጉዞ ውስጥ ያለው ቅንጫቢ የመንገድ ጉዞ ይኼው ተጀምሯል፡፡ ከመጀመሩ ከሾፌሩ ጀርባ የተቀመጡ ሁለት አካለ ደንዳና ጎልማሶች ተበሳጭተው የሚያበሳጭ ወሬ ያወራሉ፡፡ ‹‹ከእንግዲህ ምን ቀረን? በላያችን ላይ ወስነው ሲያበቁ በተወያያችሁት መሠረት ነው ይሉናል…›› ይላል አንደኛው፡፡ ‹‹ኧረ ተወኝ እባክህ፣  አዳሜ ወረዳና ክፍለ ከተማ ጉዳይ በማስፈጸም ስም ምን ሲሠራ እንደሚውል ታውቃለህ?›› ይላል የወዲያኛው፡፡ ከእነሱ ጀርባ አብሮኝ የተቀመጠ ወጣት፣ ‹‹በየዕለቱ የሚፈበረከው አጀንዳ ላይ ተጥደን ወሬ ስናሟሙቅ እንኳን መንደር አገሪቱንም ሳናስወስድ አንቀርም…›› እያለ ሁሉን አጠቃሎ የዘመኑን ሰው ባህሪ ያማልናል፡፡ ‹‹የጅምላ ፍረጃ ማብቂያው የትና መቼ ይሆን?›› የሚል የአንድ ጎልማሳ ድምፅ ይሰማናል፡፡ ‹‹ቆይ ታዲያ መጨረሻችን ምን ሊሆን ነው በዚህ ዓይነት….›› ሲል አንደኛው ጎልማሳ፣ ‹‹የእኔ ወንድም መጀመርያም መጨረሻም ብሎ ነገር የለም፡፡ ዋናው ቁምነገር የውሳኔው ቦታ ላይ ለመገኘት ብቁ መሆን ነው…›› በማለት ረቀቅ ያለ ነገር ተናገረ፡፡ ዝም ብሎ መስማት ነው!

ሦስተኛ ወንበር ላይ ከአንዲት ቀዘባ ልጅ ጋር አብሮ የተቀመጠ ተሳፋሪ፣ ‹‹የኑሮ ውድነቱን አስመልክተን ለምን ሰላማዊ ሠልፍ አንወጣም?›› ሲል እንደ አሪፍ የሳይንስ ግኝት በሐሳቡ እየታበየ ይጠይቃል፡፡ ‹‹ነገር ደህና አደርክ?›› ሲል እሰማዋለሁ በሹክሹክታ መሀል ወንበር የተቀመጠው ወጣት፡፡ ‹‹እንዴት ይመስላችኋል?›› እያለ በጥያቄ ላይ ጥያቄውን ሲያከታትል ተሳፋሪዎች በሙሉ ‹ምን ነካው ይኼ?› እያሉ ይገላምጡታል፡፡ ቆየት አለና ደግሞ አንዱ፣ ‹‹ሾፌር ቴፑ አይሠራም እንዴ? ሙዚቃ ክፈትና ገላግለን ከዚህ ሰው…›› ሲለው ሾፌሩ ፈጠን ብሎ፣ ‹‹አብሽር ምን ልጋብዛችሁ ደስ ያላችሁን…›› ብሎ ምርጫውን ለተሳፋሪዎች ቢሰጥ የተመካከሩ ይመስል ሁሉም በአንድነት፣ ‹ወይ ዘንድሮ!› ብለውት ተሳሳቁ፡፡ ምን ያድርጉ ነገሩ ሁሉ ድብልቅልቅ ሲልባቸው?

ጉዟችን እንደ ቀጠለ ነው፡፡ በዚህ መሀል አንዱ፣ ‹‹የትራንስፖርት ችግር እጅግ አሳሳቢ ደረጃ ላይ ደርሷል፡፡ ‹‹ኧረ ጎበዝ በዚህ ዓይነት እስከ መቼ ልንዘልቅ ነው?›› ሲል፣ ‹‹ማን አወቀ ብለህ ነው?›› ይለዋል ከወዲያ አንዱ፡፡ ‹‹አሁንማ የለም፣ አልቋል፣ ጠፍቷል፣ ጨመረ የሚሉት ቃላት ራሳቸው እንደ ሰለቹን ምንም አልሰለቸንም፡፡ ታክሲ ስትሉ የለም፣ ኔትወርክ ስትሉ የለም፣ መብራት ጠፍቷል፣ ውኃ ተቋርጧል፣ የእህል ዋጋ ጨምሯል፡፡ እንዲያው ምን እንደሚሻላት ይህች አገር?›› ትላለች ሦስተኛ ወንበር ላይ ያለችው ቀዘባ፡፡ ‹‹ሲሮጡ የታጠቁት ሲሮጡ ይፈታል ስለሆነ እኮ ነው የዚህ ሁሉ ችግር መንስዔ፡፡ መንግሥት ሳያስበው ዘጠኝ ድስት ጣደና አንዱን ሲለው አንዱ፣ አንዱን ሲለው ሌላው የሚያርበት፡፡ ሌላው ቢቀር የመገናኛና የመጓጓዣ ሥራዎች በቅድሚያ ሳይጠናቀቁ እንዴት ተብሎ ነው የዕድገትና የትራንስፎርሜሽን ዕቅዱ ዕውን ሊሆን የሚቻለው? እህ? ከክልል ከተሞች ወደ መሀል ከተማ የሚታየው ከፍተኛ የሕዝብ ፍልሰት ነው፣ የሕዝብ ቁጥር እየጨመረ ነው፣ ይኼ ደግሞ ዕድገትና እንቅስቃሴ ስላለ ነው…›› ብሎ ሲናገር ጎልማሳው፣ ‹‹እና መንግሥት የሚለው አያጣምና እኛ ትራንስፖርት ባጣን ቁጥር ሥቃያችን ልክ ማጣት አለበት?›› የሚለው ሌላ ነው፡፡ ‹‹በሽግግር ወቅት ላይ ስለሆንን ችግሩን መቻል ነው…›› የሚል ሌላ ድምፅ ይሰማል፡፡ ድምፃችን ይሰማ እንጂ!

መጨረሻ ወንበር ጥግ ላይ የተቀመጠ ለግላጋ ወጣት አጠገቡ ላለው ጓደኛው፣ ‹‹የዛምቢያ ፕሬዚዳንት በቀደም ዕለት የተናገሩትን ሰማህ?›› ሲለው፣ ‹‹ትቀልዳለህ እንዴ? ካላጣሁት የዛምቢያን ፕሬዚዳንት ወሬ ልቃርም ወይ…›› ብሎ ሲመልስለት፣ ‹‹ወንድሜ ተረጋጋ፣ ሰውየው በቀደም ሚኒስትሮቻቸውንና የከተማ ከንቲባዎችን ሰብስበው የተናገሩት ለእኛ አገርም ጠቃሚ ስለሆነ ነው ልነግርህ የፈለግኩት›› አለው፡፡ ይኼኔ የሁሉም ተሳፋሪዎች ጆሮ ወደ እሱ ሲቀሰር ወያላው፣ ‹‹እባክህ ንገረን…›› ብሎ አደፋፈረው፡፡ እሱም የብዙዎችን ትኩረት ማግኘቱን ሲረዳ፣ ‹‹የዛምቢያ ፕሬዚዳንት በተለይ ከንቲባዎችን በገበያ ሥፍራ መፀዳጃዎችን መገንባት ሲገባችሁ፣ የቅንጦት መኪና ለመግዛት ትሽቀዳደማላችሁ፡፡ ለአንድ ቪ ኤይት መኪና በመቶ ሺዎች ዶላር እያወጣችሁ ከምትገዙ ለሕዝብ አገልግሎት የሚሰጡ ፕሮጀክቶችን ለምን አትሠሩም? ቪ ኤይት ያማረው በገዛ ገንዘቡ ገዝቶ ይንዳ ነበር ያሉት…›› ብሎ ንግግሩን ሲቋጭ እኚያ እናት፣ ‹‹ድንቄም፣ ቪ ኤይት ያማረው ሁሉ በዘረፈው እንጂ ከየት ባመጣው ገንዘብ ነው የሚገዛው… ወሬኛ ሁሉ…›› ሲሉ ከመሳቅ በስተቀር ምንም መልስ አልነበረም፡፡ ከየት መጥቶ!

ወደ መዳረሻችን እየተቃረብን ነው፡፡ ታክሲያችን ፒያሳ ደርሶ ሲቆም ከርቀት የሰዎች ድምፅ ያስተጋባል፡፡ ከወዲያ በኩል የሚሰማው ድምፅ የተለመደው ዓይነት ሳይሆን የሰላማዊ ሠልፍ መፈክር ይመስላል፡፡ እኛ ተሳፋሪዎች በመስኮት አንገታችንን አስግገን ሳናዳምጥ፣ ‹‹ይመዝገብልን… ይመዝገብልን….›› የሚል ድምፅ ያስተጋባል፡፡ ወያላው ወረድ ብሎ በአካባቢው ከሚገኙ ሰዎች ጋር ተነጋግሮ ሲመለስ በሳቅ እየተንፈራፈረ ነበር፡፡ ሾፌሩ፣ ‹‹ምንድነው የሚያስቅህ?›› ሲለው፣ ‹‹ይመዝገብልን የተባለው ጉዳይ ነው ያሳቀኝ…›› ብሎት ሳቁን ቀጠለ፡፡ አንዲት እናት፣ ‹‹ምኑ ነው የሚመዘገበው?›› ሲሉት፣ ‹‹አንዱ ወፈፍ ያደረገው ከመስከረም ጀምሮ ሰላም እንዲሰፍን ፀሎት ለማደርግበት ገንዘብ ስጡኝ ሲላቸው፣ ከየትኛው አጥቢያ እንደመጣ አስመዝግብ እያሉት ነው…›› ሲላቸው ከወያላው ይበልጥ የተሳፋሪዎች ሳቅ ታክሲዋን አንዘፈዘፋት፡፡ እኚያ እናት አሁንም፣ ‹‹ነገሩ እንዲህ ነው? በፈጣሪ ዘመን አጭበርባሪው በበዛበት በዚህ ዘመን ጥሩ ማሳሰቢያ ነው፡፡ በሉ እናንተም እንዳትረሱ መዝግቡ…›› ሲሉን ታክሲያችን መቆሚያዋ ደረሰች፡፡ ወያላው በሩን ከፍቶ ‹‹መጨረሻ›› በማለት ሲያሰናብተን የምዝገባው ነገር እያነጋገረን ነበረ፡፡ የዘንድሮን ነገር እንመዝግብ እንጂ፡፡ መልካም ጉዞ!

Latest Posts

- Advertisement -

ወቅታዊ ፅሑፎች

ትኩስ ዜናዎች ለማግኘት