Sunday, March 26, 2023
- Advertisment -
- Advertisment -

የብሽሽቅ ፖለቲካ ውጤቱ ኪሳራ ነው!

በኢትዮጵያ ነባራዊ ሁኔታ ጠቃሚ የሆኑና ያልሆኑ ጉዳዮችን የመለየት ችግር በስፋት እየተስተዋለ ነው፡፡ የትኛው ከየትኛው ቢቀድም ለዕድገት ይጠቅማል ከማለት ይልቅ፣ በዘፈቀደ የሚከናወኑ ነገሮች እየበዙ ነው፡፡ ምክንያታዊ ሆኖ በማስተዋል መመራት እየተቻለ፣ በስሜታዊነት በሚወሰዱ ዕርምጃዎች ሳቢያ ቅራኔ የሚፈጥሩ ጉዳዮች ቁጥራቸው እየጨመረ ነው፡፡ አገር ወደፊት እንዳትራመድ ከሚያደርጉ አዋኪ ነገሮች መሀል በሚገባ ማቀድ አለመቻል፣ ሳያቋርጡ ስለትናንት ሁነቶች ብቻ ማሰብ፣ ለአሉታዊ መረጃዎች ትኩረት መስጠት፣ በሌሎች ላይ ጥገኛ መሆን፣ የማኅበራዊ የትስስር ገጾች እስረኛ መሆን፣ እርስ በርስ አለመስማማት፣ ራስን ከሌሎች ጋር ተገቢ ባልሆኑ ጉዳዮች ማወዳደር፣ ተቃርኖ የሚፈጥሩ ጉዳዮችን ማግዘፍና የመሳሰሉት ይጠቀሳሉ፡፡ ፖለቲካው የሚመራው በብሽሽቅ በመሆኑ ብቻ ከሐሳብ ልዕልና በላይ ጎልቶ የሚሰማው አሽሙርና ስድብ ነው፡፡ ለአገር ዕድገት የሚጠቅሙ ሐሳቦች ላይ ማተኮር እያቃተ፣ አብዛኛው ጊዜና ጉልበት የሚባክነው ፋይዳ ለሌላቸው ጉዳዮች ነው፡፡ ለአገር የሚጠቅሙ ብርቱ ሐሳቦች ከመሀል እየተገፉ ብሽሽቅ የአገሪቱን የፖለቲካ ምኅዳር ሲቆጣጠር፣ ብሔራዊ ምክክርም ሆነ ድርድር ለማድረግ የሚኖረው ተስፋ ጉዳይ ያሳስባል፡፡

ብልጥ ፖለቲከኞች በአገኙት አጋጣሚ ሁሉ የሚፈልጉትን መልዕክት ማስተላለፋቸው አዲስ ነገር አይደለም፡፡ አጋጣሚው ይገኝ እንጂ ወቅቱን የሚዋጅ ወይም ፍላጎታቸውን የሚያንፀባርቅ ንግግር ማድረጋቸውም የሚጠበቅ ነው፡፡ ከብልጠቱም ሆነ የተገኘ አጋጣሚን ለመጠቀም ዳተኛ ወይም ቀርፋፋ የሆኑት ደግሞ፣ እንኳንስ ፍላጎታቸውን ለማስተጋባት ሌሎች የሚሉትን ለማዳመጥ ዝግጁ አይደሉም፡፡ በዚህም ምክንያት አጀንዳ ከመቅረፅና ከማሠራጨት ይልቅ፣ የሌሎች አጀንዳ አራጋቢ ሆነው ይቀራሉ፡፡ በኢትዮጵያ ወቅታዊ ፖለቲካ ውስጥ እየተስተዋሉ ካሉ በጣም አሳሳቢ ጉዳዮች ውስጥ፣ አጀንዳ ሰጪውና ተቀባዩ ያሉበት ርቀት ከመጠን በላይ መለጠጡ ነው፡፡ ከአጀንዳ ሰጪው ወገን በማያቋርጥ ሁኔታ የተለያዩ መልዕክቶች በተለያዩ ይዘቶችና ቅርፆች ሲተላለፉ፣ ከተቀባዩ ወገን ያለው ተመሳሳይ ማባሪያ የሌለው ንትርክ ፖለቲካውን እያደር ቁልቁል እየሰደደው ነው፡፡ የኢትዮጵያ ፖለቲካ በዚህ ሁኔታ ወደፊት ይራመዳል ለማለት በሚያዳግት ነባራዊ ሁኔታ ውስጥ፣ የአጀንዳ ተቀባዩ ባህሪ መለወጥ ካልቻለ ባለህበት እርገጡ በሚያሳዝን ሁኔታ መቀጠሉ አይቀሬ ነው፡፡ የቃላት ብሽሽቅ ላይ የተቸከለ የፖለቲካ ምኅዳር ውስጥ ሆኖ ለውጥ መጠበቅ ፈፅሞ አይቻልም፡፡

ኢትዮጵያ ለላፉት ሁለት ዓመታት ያህል ከነበረችበት አውዳሚ ጦርነት ውስጥ ወጥታ ሰላም መስፈን ሲገባው፣ አሁንም በሚያሳዝን ሁኔታ ወደ ጦርነቱ የሚመልሱ ምልክቶች እየታዩ ነው፡፡ ማንም ጤነኛ አስተሳሰብ ያለው ሰው ጦርነትን እንደገና ለዓላማ ማስፈጸሚያ ማድረግን ይደግፋል ተብሎ አይታሰብም፡፡ ያ ሁሉ ዕልቂት፣ ውድመት፣ መፈናቀልና ሥቃይ ታልፎ ጦርነት ሊነሳ ይችላል የሚል ሥጋት ሲፈጠር ያሳዝናል፡፡ ሰላምን ለማስፈን ያሉ አማራጮችን በቀኝም በግራም አማትሮ መፍትሔ ላይ ለመድረስ መማሰን ሲገባ፣ ለጦርነት ታጥቆ መነሳት የሚያገለግሉ የተቃርኖ ግብዓቶችን ማሰባሰብ ከጤነኛ አዕምሮ የሚጠበቅ አይደለም፡፡ ለአገር ፋይዳ በሌላቸው ነገሮች በመተነኳኮስ የቃላት ጦርነት ውስጥ ከመግባት ጀምሮ፣ አገር ሊያፈርስ የሚችል አውዳሚ ውጊያ ለመጀመር ማሰፍሰፍ የሚጠቅመው ታሪካዊ ጠላቶችን ብቻ ነው፡፡ እነሱ ደግሞ ይህንን አጋጣሚ ለመጠቀም ኢትዮጵያውያንን በሚችሉት ሁሉ ይከፋፍላሉ፡፡ አጀንዳ ሰጪው አስከፊ ንግግር እንዳያደርግና ተቀባዩ እንዳይከፋ ጥንቃቄ መደረግ አለበት፡፡ የፖለቲካ አቋም ልዩነት ተከብሮ መፎካከር የሚቻለው፣ በመከባበር ላይ የተመሠረተ የፖለቲካ ምኅዳር እንዲፈጠር የጋራ ጥረት ሲደረግ ነው፡፡

የአገሪቱ የፖለቲካ ፓርቲዎች ድክመት በፖለቲካ ምኅዳሩ ውስጥ ለሚስተዋሉ እያደር ማነሶች ትልቅ አስተዋፅኦ እንዳለው መካድ አይቻልም፡፡ በጣም ከተወሰኑ የፖለቲካ ፓርቲዎች በስተቀር አብዛኞቹ እንደሌሉ ነው የሚቆጠሩት፡፡ አሉ ከሚባሉት ውስጥም ቢሆን እየታየ ያለው መፍረክረክ ድክመቱን እያጠናከረው ነው፡፡ ብዙዎች ከፍተኛ የሆነ የፋይናንስ እጥረት ስላለባቸው ከበስተጀርባቸው ሆነው ለሚዘውሯቸው ጉዳይ አስፈጻሚ ሆነዋል፡፡ በስንት ልፋት የሚገኘው የድጎማ ገንዘብ ፓርቲዎቹን ከማጠንከር ይልቅ የንትርከ ምንጭ ይሆንባቸዋል፡፡ በዚህም ምክንያት በአኩራፊዎች ስብስብ የሚመሠረቱ ፓርቲዎች ዕድሜያቸው ያጥራል፣ ወይም ቀንጭረው ይቀራሉ፡፡ በዚህና በሌሎች መሰል ምክንያቶች የፖለቲካ ምኅዳሩ የሐሳብ ድርቅ ገጥሞታል፡፡ በአገሪቱ ዙሪያ ገብ ጉዳዮች ላይ አቅጣጫ ማመላከት የሚገባቸው ፓርቲዎች እየሟሙ፣ የፖለቲካ ምኅዳሩ የተሞላው በማኅበራዊ የትስስር ገጾች ተንታኞችና አስተንታኞች ነው፡፡ እዚህ ሠፈር ውስጥ ካሉት ብዙዎቹ ምንም ዓይነት ኃላፊነት የማይሰማቸው፣ ከኋላ ሆነው የሚገፏቸውን ቀለብ ሰፋሪዎች ፍላጎት ለማስፈጸም የሚሯሯጡና በአገኙት አጋጣሚ ሁሉ ተቃርኖውን ለማስፋፋት የሚቅበዘበዙ ናቸው፡፡ የፖለቲካ ምኅዳሩ በሐሳብ ድርቅ እየተጠቃ ብሽሽቁ የተስፋፋው በዚህ ሳቢያ ነው ቢባል ማጋነን አይሆንም፡፡

ኢትዮጵያ በተለያዩ ምክንያቶች ከባድ ውጥንቅጥ ውስጥ ሆና ልዩነትን ይዞ በብሔራዊ ጉዳዮች ላይ መስማማት እየተቻለ፣ ከሦስት ቀናት በላይ ዕድሜ የሌላቸው የንትርክ አጀንዳዎች ላይ መጣድ ተገቢ አይደለም፡፡ ኢትዮጵያ መልማትና ማደግ የምትችለው ልጆቿ ልዩነታቸውን ይዘው የሐሳብ ፍልሚያው ላይ ሲያተኩሩ ነው፡፡ የሐሳብ መፋለሚያ ሜዳው ላይ በጨዋና በታረመ ቋንቋ መነጋገር ሲቻል፣ ለሐሳብ ልዕልና የሚደረገው ፉክክር ፈር ይይዛል፡፡ ሕጋዊና ሰላማዊ የፖለቲካ ፉክክሩ የብዙኃንን ቀልብ ሊገዛ የሚችለው፣ ለሕገወጥነትና ለሥርዓተ አልበኝነት የሚዳርጉ ብሽሽቆች ሲወገዱ ነው፡፡ አሁን በግልጽ እንደሚታየው ከአንድ ሥፍራ አንድ መናኛ አጀንዳ ሲለቀቅ፣ ከዳር እስከ ዳር ከሚያስተጋቡት ጀምሮ ውለው የሚያድሩበት ድረስ የሚጠፋው ጊዜና ጉልበት ያሳዝናልም፣ ያስተዛዝባልም፡፡ ይህንን ችግር በውል ተገንዝበው መፍትሔ መፈለግ የሚገባቸው የአገሪቱ የፖለቲካ ልሂቃንም ሆኑ ምሁራን፣ ልዩነቶቻቸውን መልክ አስይዘው የሚበጀውን መፍትሔ ማፍለቅ ይጠበቅባቸዋል፡፡ አንድ አጀንዳ ሲለቀቅ ራስን እዚያ ውስጥ ከቶ መብሰልሰል ፋይዳ ቢስ ነው፡፡ ቢዘገይም አልረፈደምና ነቃ ማለት ተገቢ ነው፡፡

በኢትዮጵያ ፖለቲካ ውስጥ አሁንም ድረስ እንደ አንድ ችግር የሚታየው ጉዳይ ካለፉ ስህተቶች ለመማር ፈቃደኛ አለመሆን ነው፡፡ ሥልጣን ላይ የወጡ ከእነሱ በፊት የነበሩት በፈጠሩት ስህተት ወይም ጥፋት ምክንያት ምን እንደ ደረሰባቸው ለማጤን በአብዛኛው ፍላጎት አይታይባቸውም፡፡ ሥልጣን ለመያዝ የሚፈልጉትም ቢሆኑ ከእነሱ በፊት የነበሩት ያልተሳካላቸው በምን ምክንያት እንደሆነ ለመረዳት አይፈልጉም፡፡ አንዱ ከሌላው ጥፋት ወይም ውድቀት እየተማረ የተሻለ ነገር ማሳየት ሲገባው፣ ራሱ መልሶ የሌላውን ስህተት ሲደግም ማየት ከማስገረም አልፎ ያሳዝናል፡፡ በዘመነ ነጭና ቀይ ሽብር ተዋንያን የነበሩ ጭምር “ዓይኔን ግንባር ያድርገው” እያሉ ጥፋታቸውን ማመን ስለማይፈልጉ፣ በዚህ ዘመን ያሉ የፖለቲካ ተዋንያን ያንን ዓይነት የውድመት መንገድ እየተከተሉ ነው፡፡ ፖለቲካው ከአራት አሥርት ዓመታት በኋላም እያደር የሚቀነጭረው ስህተትን መደጋገም ልማድ በመሆኑ ነው፡፡ በዚህ ሁኔታስ አገራዊ ምክክሩ እንዴት ወደፊት ሊራመድ ይችላል ተብሎ ካልታሰበበት፣ የብሽሽቅ ፖለቲካው የበላይነቱን እየያዘ ውድቀቱ እየተባባሰ ይቀጥላል፡፡ ለአገር ፋይዳ የሌላቸው ከንቱ አጀንዳዎች ብሽሽቁን እያፋፋሙ የሚያስከትሉት ኪሳራ ነው!

በብዛት የተነበቡ ፅሁፎች

የአየር መንገድ ተጓዦች በሻንጣ የሚያስገቡትን የልብስና የጫማ ብዛት የሚገድብ ረቂቅ መመርያ ተዘጋጀ

ከቀረጥ ነፃ ይገቡ የነበሩ ዕቃዎች 87 በመቶ እንዲቀንሱ ተደርጓል መንገደኞች...

ግራ አጋቢው የኤሌክትሪክ መኪና ጉዳይ

በያዝነው ዓመት መጀመሪያ በወርኃ ጥቅምት የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ 39...

ነባር ‹‹ላዳ›› ታክሲዎችን መሸጥና መለወጥን ጨምሮ ለሌላ ማስተላለፍ ተከለከለ

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በተለምዶ ‹‹ላዳ ታክሲ›› ተብለው የሚታወቁትን...

አብን በደቡብ አፍሪካ የሚደረገው የሰላም ንግግር ይሳካል የሚል እምነት እንደሌለው ገለጸ

የፌዴራል መንግሥትና ሕወሓት ካለፈው ሳምንት ጀምሮ በደቡብ አፍሪካ ፕሪቶሪያ...
- Advertisment -

ትኩስ ፅሁፎች

ለፋይናንስ ዘርፉ ብቃት ያለው የሰው ኃይል የማፍራት የቤት ሥራን የማቃለል ጅማሮ

የአገሪቱ የፋይናንስ ዘርፍ እያደገ ለመሆኑ ከሚቀርቡ ማስረጃዎች ውስጥ  የግል...

የምድር ባቡርን የሚያነቃቃው የመንግሥት ውሳኔ

በኢትዮጵያ ወደብ አልባነት ላይ የተደመረውን የሎጀስቲክስ ችግር ለመፍታት ግዙፍ...

የፓርላማ አባላት ስለሰላም ስምምነቱ አፈጻጸም ግልጽ መረጃ የለንም አሉ

‹‹ሕወሓትን ለፍረጃ አብቅተውት የነበሩ ጉዳዮች በአብዛኛው መልክ ይዘዋል›› ሬድዋን...

ብሔራዊ ባንክ የፖሊሲ ማሻሻያዎችን ይፋ ሊያደርግ ነው

የፋይናንስ ዘርፉን ለማረጋጋት የሚረዳ ሪፎርም ማጠናቀቁን የገለጸው የኢትዮጵያ ብሔራዊ...
spot_img

ተዛማጅ ፅሁፎች

ግልጽነትና ተጠያቂነት የጎደለው አሠራር ለአገር አይበጅም!

ሰሞኑን የአሜሪካና የኢትዮጵያ መንግሥታት በሰሜን ኢትዮጵያ ጦርነት ተፈጽመዋል በተባሉ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶችና የጦር ወንጀሎች መግለጫ ላይ አልተግባቡም፡፡ አለመግባባታቸው የሚጠበቅ በመሆኑ ሊደንቅ አይገባም፡፡ ነገር ግን...

የምግብ ችግር ድህነቱን ይበልጥ እያባባሰው ነው!

በአገር ውስጥና በውጭ የተለያዩ ተቋማት የሚወጡ መረጃዎች እንደሚያሳዩት፣ በአሁኑ ጊዜ በኢትዮጵያ ከ22 ሚሊዮን በላይ ዜጎች አስቸኳይ የምግብ ዕርዳታ ያስፈልጋቸዋል፡፡ እነዚህ ወገኖች በሰሜን ኢትዮጵያ ጦርነት፣...

መብትና ነፃነትን የሚጋፉ ድርጊቶች ይወገዱ!

ኢትዮጵያውያን በየትኛውም የአገሪቱ ክፍል የመዘዋወር፣ የመኖር፣ የመሥራትና ሀብት የማፍራት ሕጋዊ መብት አላቸው፡፡ ይህ መብት በግልጽ የተደነገገው በሥራ ላይ ባለው ሕገ መንግሥት ሲሆን፣ አሁንም ሕገ...