ፋሲል ከነማና ድሬዳዋ ከተማ በዲሲፕሊን ጥሰት ተቀጡ
በኢትዮጵያ እግር ኳስ ጎልተው ከሚነገሩ ዓበይት ጉዳዮች መካከል የክለቦች የፋይናስ ሥርዓት ይጠቀሳል፡፡ በየዓመቱ ውድድሮች ተጀምረው ብዙም ሳይራመዱ የተጨዋቾችን ‹‹ወርኃዊ ክፍያ መክፈል አልቻሉም›› በሚል ወቀሳ ሲቀርብባቸው የሚደመጡ ክለቦች፣ ሃይ ባይ ባጣው የፋይናስ ሥርዓት ‹‹ለተጨዋቾች ዝውውር›› በሚል ከወዲሁ ሚሊዮኖችን ማውጣት መጀመራቸው አነጋጋሪ ሆኗል፡፡
በኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን የተጫዋቾች ውውር መመርያ መሠረት የፕሪሚየር ሊግ ክለቦች የ2015 የውድድር ዘመን የመጀመርያ ዝውውር ጊዜ ከሐምሌ 1 ቀን 2014 እስከ መስከረም 19 ቀን 2015 ዓ.ም. ድረስ እንደሚሆን ይፋ አድርጓል፡፡
ይህንኑ ተከትሎ ሁሉም ክለቦች በዝውውር ገበያው ተሳትፎ እያደረጉ ይገኛል፡፡ የዝውውር ገበያውን በሚመለከት የሚወጡ መረጃዎች እንደሚያመላክቱት ከሆነ፣ በአሁኑ ወቅት ለአንድ ተጨዋች ዝውውር ትንሹ ክፍያ አራት ሚሊዮን ብር ሲሆን፣ ትልቁ ደግሞ ስምንት ሚሊዮን ብር ደርሷል፡፡
ሪፖርተር በዚህ ጉዳይ የክለብ አመራሮችን ጨምሮ የተለያዩ ባለድርሻ አካላትን አነጋግሯል፡፡ ይሁንና ግን ሁሉም ለዝውውር ገበያው ማሻቀብ ምክንያት በሚሉት ጉዳይ ላይ ማንነታቸውን ገልጸው ለመናገር ፈቃደኛ አይደሉም፡፡ ምክንያታቸው ደግሞ በቀጣዩ ውድድር ዓመት ክለቦቻቸው የሚፈልጓቸውን ተጨዋቾችንም ሆነ አሠልጣኞችን ለማግኘት ዕድል ስለማያገኙ በመሆኑ እንደሆነ የሚናገሩ ግን አልጠፉም፡፡
በዚህ ጉዳይ የክለብ አመራሮችም ሆኑ ጉዳዩ የሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ችግሩን መናገር የማይፈልጉት በዋናነት የዝውውር ገበያው መሪ ተዋንያን በመሆናቸው እንደሆነ በሌላ በኩል የሚናገሩ አሉ፡፡ ምክንያቱም የሚሉት እነዚሁ አካላት፣ ‹‹በ2014 ውድድር ዓመት ከጥቂት ክለቦች በስተቀር ብዙዎቹ ውል ላላቸው ተጨዋቾች ወርኃዊ ክፍያ መክፈል ተስኗቸው ክስ ሲቀርብባቸው የነበሩ ናቸው፡፡ አሁን ላይ የዝውውር ገበያው ተከፈተ በተባለበት ቅፅበት ገንዘቡን ከየት አምጥተውት ነው ሚሊዮኖችን ለተጨዋቾች ዝውውር የሚያውሉት፤›› በማለት ይጠይቃሉ፡፡
በአሁኑ ወቅት በፕሪሚየር ሊግ እየተሳተፉ ከሚገኙ ክለቦች መካከል ቅዱስ ጊዮርጊስ አልያም ኢትዮጵያ ቡና ካልሆኑ በስተቀር (የሊጉ አክሲዮን ማኅበር የሚከፍላቸው እንደተጠበቀ ሆኖ) ሁሉም ክለቦች በአንድም ሆነ በሌላ በጀታቸው ከመንግሥት ቋት መሆኑን የሚናገሩት አስተያየት ሰጪዎቹ፣ ‹‹መንግሥት አልያም የሚመለከተው አካል በአገሪቱ አንድ እንኳ የበቃ ስታዲየም በሌለበት ሁኔታ በቴክኒካል ብቃት ሳይሆን ማሊያ ለሚቀያይሩ ዕድሜ ጠገብ ተጨዋቾች እስከ ስምንት ሚሊዮን ብር ‹‹ፊርማና ማትጊያ›› በሚል የሚፈሰውን የሕዝብ አንጡራ ሀብት የመፍትሔ አቅጣጫ ሊያበጅለት ይገባል፤›› ይላሉ፡፡
በሌላ ዜና የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ውድድር አመራርና ሥነ ሥርዓት ኮሚቴ ረቡዕ ሰኔ 29 ቀን 2014 ዓ.ም. ባደረገው ስብሰባ፣ በውድድር ዓመቱ በተደረጉ ውድድሮች፣ ከዳኞችና ታዛቢዎች የቀረበለትን የዲሲፕሊን ሪፖርት መርምሮ በሁለት ክለቦች ላይ የዲሲፕሊን ዕርምጃ መውሰዱን ይፋ አድርጓል፡፡
በኮሚቴው ውሳኔ መሠረት የድሬዳዋ ከተማ እግር ኳስ ክለብ ከባህር ዳር ከተማ እግር ኳስ ክለብ ጋር በ28ኛው ሳምንት ጨዋታ ላይ የክለቡ ደጋፊዎች፣ የውድድር አመራሮችን ‹‹አፀያፊ ስድብ ተሳድበዋል›› በሚል፣ በፌዴሬሽኑ የዲሲፕሊን መመርያ ክፍል ሦስት አንቀጽ 66 መሠረት፣ ክለቡ 75 ሺሕ ብር ቅጣት እንዲከፍል መወሰኑን አስታውቋል፡፡
በተመሳሳይ የፋሲል ከነማ እግር ኳስ ክለብ ደጋፊዎች፣ በ30ኛው ሳምንት ጨዋታ ላይ ‹‹ስፖርታዊ ጨዋነትን ያልተከተለ ድጋፍ አድርገዋል›› በሚል ኮሚቴው ፋሲል ከነማ፣ 100 ሺሕ ብር ቅጣት እንዲከፍል የፕሪሚየር ሊጉ የዲሲፕሊን ኮሚቴ ወስኗል፡፡